Entertainment  | Mutimedia | Educational
Welcome
Login / Register

Daniel Kibret-ዝኆኑም ትንኙም

አንበሳ በሚገዛው አንድ ጫካ ውስጥ አያሌ እንስሳት ይኖሩ ነበር፡፡ አንድ ቀን አንበሳ ለአንድ የሥራ ጉዳይ ወደ ሌላ ሀገር ለመሄድ ተነሣ፡፡ የእርሱ መሄድ በእንስሳቱ ዘንድ በተሰማ ጊዜ የጫካውን ሕልውና በተመለከተ ጥያቄ ተነሣ፡፡ ጦሩን ማን ይመራል? ገንዘብ ማን ይይዛል? ምግብ ማን ያከፋፍላል? መልእክት ማን ይቀበላል? ዳኝነት ማን ይሰጣል? ሠራተኛ ማን ያሠማራል? ሹመት ማን ይሰጣል? እያሉ እንስሳቱ መጠያየቅ ጀመሩ፡፡ በዚያ ጊዜ አንበሳ ሁሉንም ነገር ጠቅልሎ ይዞት ስለነበር አሁን እርሱ ሲሄድ ነገር ዓለሙ ሁሉ ሊዛባ ደረሰ፡፡
አንበሳ ችግሩን ቢረዳውም ነገር ግን ለአንዱ እንስሳ ብቻ ሥልጣኑን ሰጥቶ መሄዱ እስከ ዛሬ ድረስ ከእርሱ በታች እኩል ሆነው የኖሩትን ታማኞቹን ማባላት መስሎ ታየው፡፡ ስለዚህም ‹ሥልጣን በተርታ ሥጋ በገበታ› ብሎ ሥልጣኑን ቆራርሶ ለሁሉም በየዐቅማቸው ለማካፈል ወሰነ፡፡ በዚህም መሠረት ነበርን የጦር ሚኒስትር፣ ዝንጀሮን ዋና ዳኛ፣ ጦጣን የገንዘብ ተቆጣጣሪ፣ ቀበሮን የሥጋ ኃላፊ፣ ዝሆንን ምግብ አከፋፋይ፣ አጋዘንን የሠራተኞች ተቆጣጣሪ፣ ተኩላን ፖሊስ አድርጎ ሰየማቸው፡፡ 
ሁሉም የጫካው እንስሳት ሹመት ሲደርሳቸው ሁለት እንስሳት ግን ምንም ሳያገኙ ቀሩ፡፡ ኤሊ እና ጥንቸል፡፡ አንበሳውም ‹‹ዔሊ እጅግ ዘገምተኛና ዛሬ ተነሥታ የዛሬ ሳምንት የምትደርስ ፍጡር ናት፡፡ ለእርሷ ሹመት መስጠት ማለት በሹመት ላይ መቀለድ ማለት ነው›› ሲል እንስሳቱ ሁሉ ሳቁ፡፡ ወደ ጥንቸልም ዞር ብሎ ‹አንቺ ሚጢጢ ፍጡር አሁን ላንቺ ሥልጣን ቢሰጥሽ ምን ታደርጊበታለሽ›› ሲል ተሳለቀባት፡፡ ይህም በእንስሳቱ ሳቅ ላይ ሌላ የሳቅ ዳረጎት ጨመረላቸው፡፡
አንበሳውም ወደ ጉዳዩ ሄደ፡፡
አንበሳው ከሄደ በኋላ የአንበሳን አለመኖር ያዩ የሩቅ ጎረቤቶቻቸው በእንስሳቱ ላይ ጦርነት ከፈቱባቸው፡፡ ይህ ጦርነት ከብዙ ዘመን በኋላ የተከሰተ ነበር፡፡ ነብር የጦር ሚኒስትር ሲሆን የመጀመርያው ነበርና የሚይዘውንና የሚጨብጠውን አጣ፡፡ በአንድ በኩል ወታደር ሲያሰለጥን በሌላ በኩል ሲዋጋ ጦርነቱን መቋቋም አቃተው፡፡ ምግብ አከፋፋዩም ምግቡን ከማከፋፋሉ በፊት በጠላት ተማረከበት፤ ዳኛውም ከነመንበሩ ተያዘ፡፡ ጦርነቱም እየገፋ መጥቶ መሐል ጫካው ላይ ደረሰ፡፡
የጎረቤት አራዊት ያንን ጫካ የወረሩበት ምክንያት ወዲያው ነበር የታወቀው፡፡ እዚያ ጫካ ያሉ እንስሳት ለብዙ የችግር ዘመን የሚሆን እህል ማከማቸታቸው ይነገራል፡፡ ይህ እህል ያለበት ቦታ በካርታ ላይ ሠፍሮ በአንበሳው እጅ ነው የሚገኘው፡፡ አሁን አንበሳ ከሄደ ደግሞ ከሹመኞቹ ለአንዱ ስለሚሰጠው ጫካውን ወርሮ እህሉን መዝረፍ ነበር ዓላማቸው፡፡
ይህ የእህሉ ካርታ በዳኝነት የተሰየመው ዝንጀሮ ጋ መኖሩ ተወርቷል፡፡ ዝንጀሮ ግን ማንበብና መጻፍ አይችልም ነበር፡፡ አንዳንድ እንስሳትም ዝንጀሮ የተሾመው በትከሻውና ለአንበሳው በዛፍ ጫፍ ላይ የሚገኝ ጣፋጭ ፍሬ እያመጣ እጅ መንሻ በመስጠቱ ነው እያሉ ያሙት ነበር፡፡ እንዲያውም ወዲያው እንደተሾመ በፈረደው ፍርድ ተከሳሹን ትቶ በስሕተት በከሳሹ ላይ እንደፈረደበት ይነገራል፡፡ ለምን እንዲህ እንዳደረገ ሲጠየቅም ‹‹ዋናው ፍርድ መሰጠቱ እንጂ በማን ላይ መፈረዱ አይደለም፤ ሪፖርት የሚቀርበውኮ ይህንን ያህል ፍርድ ተሰጠ ተብሎ እንጂ በእነ እገሌ ላይ ተፈረደ ተብሎ አይደለም›› ማለቱ ተወርቷል፡፡ በዚያም ምክንያት ‹እርሱ ዘንድ ከስሶ ከመሄድ ተከስሶ መሄድ ይሻላል› እየተባለ እስከ መነገር መድረሱን የሚናገሩ አሉ፡፡
ዝንጀሮው ተይዞ የእህሉን ቦታ የሚያሳየውን ካርታ ሲጠየቅ ግን ካርታ መጫወት እንጂ ካርታ ማንበብ እንደማይችል ነበር በኀዘን የገለጠው፡፡ ይህንንም ቦታ ሊያገኘ የቻለው ከታላላቆች ጋር ካርታ በመጫወቱና በማንኛውም ጊዜ ተጠንቅቆ በመሸነፉ መሆኑን ተናግሯል፡፡ ከታላላቆች ጋር በሚደረግ የካርታ ጨዋታ ጥንቃቄ መደረግ ያለበትም ላለመሸነፍ ሳይሆን ላለማሸነፍ መሆን እንዳለበትም መክሯል፡፡
እርሱ ዘንድ የለም የተባለው ካርታ ምናልባት ገንዘብ ቤቷ ጦጣ ጋር ሊኖር ይችላል ተብሎ ተፈልጎ ነበር፡፡ ጦጣ ግን ልትገኝ አልቻለችም፡፡ አንዳንድ ምርኮኛ የሆኑ እንስሳትም ጦጣ ገንዘቡን ከመቆጣጠር ይልቅ ገንዘቡ ሳይቆጣጠራት እንዳልቀረ ገምተዋል፡፡ ገንዘቡንም ወደ ሌላ ጫካ ሳታዞረው እንዳልቀረች ይጠራጠራሉ፡፡ ለብዙ ዘመናት ከዚያ ጫካ ወጥታ የማታውቀው ጦጣ ሰሞኑን የውጭ ጉዞ ማብዛቷንና ከአካባቢው ጫካዎች በአንዱ ደግሞ ገንዘብ ቆጥራ ስትከፍል መታየቷ ይወራል፡፡ አሁንም የጠፋችው ወደዚያው ሄዳ ሊሆን እንደሚችል የሚገምቱ አሉ፡፡
ዝሆኑ ስለ ካርታው የሚያውቀውም ሆነ እህል ስለ መከማቸቱ የሰማው ነገር የለም፡፡ እርሱ ስለ ጫካው አስቦ እንደማያውቅ ይነገራል፡፡ ከአንዲት ሚስቱና ከሦስት ቡችሎቹ ጋር የሚኖርባት አካባቢ አለችው፡፡ እርሱም ከዚያ አካባቢ መውጣት አይፈልግም፤ ሌላ እንስሳም ወደ አካባቢው አያስጠጋም፡፡ ለርሱ ጫካው ማለት መንደሩ ብቻ ነው፡፡ አሁንም የጎረቤት አራዊት ጫካውን ሲወርሩት እርሱ ቁብ አልሰጠውም፡፡ ለእርሱ ጦርነቱ ተጀመረ የሚለው እርሱ መንደር ጦርነቱ ሲደርስ ብቻ ነው፡፡ አንዳንዶቹን እንስሳት ያሳቀቸው ነገር ቢኖር ዝሆኑ ከጥቂት ቀናት በላይ የሚመገበው ነገር እንደሌለውና ምግቡን የሚያገኘው ከሌሎች አካባቢ መሆኑን አለመረዳቱ ነው፡፡
ቀበሮም ቢሆን ጦርነቱ አላስጨነቀውም፡፡ እንዲያውም ከጦርነቱ እንዴት ማትረፍ እንደሚችል እያሰበ ነበር፡፡ ቀበሮ ‹አንዱ ሲሞት አንዱ ይወለዳል፤ አንዱ ሲዳር አንዱ ይሞታል› የሚባል አባባል አለው፡፡ ስለዚህም በጫካው ውስጥ አንድ ችግር ሲከሰት ችግሩን እንዴት እንደሚፈታው ማሰብ ቀበሮን አይመለከተውም፡፡ እርሱ የሚያስበው ከችግሩ እንዴት ማትረፍ እንደሚቻል ነው፡፡
እንዲያውም አንዳንዶች የሚከተለውን ነገር ማሳያ ነው ብለው ይናገሩለታል፡፡
አንድ ጊዜ በጫካው የሚገኘው ወንዝ ተበከለና ብዙ እንስሳት ሞቱ፡፡ ወንዙ ከሁለት አቅጣጫ መጥቶ ጫካው ድንበር ላይ ሲደርስ አንድ ይሆናል፡፡ ቀበሮም በሽታው ሳያስጨንቀው ወዲያውኑ መድኃኒት ዐዋቂ ነኝ ብሎ መድኃኒት መቸብቸብ ጀመረ፡፡ እንስሳቱ ሁሉ በሽታውን ስለፈሩት በውድ ዋጋ ያንን ያልታመነ መድኃኒት እየገዙ መውሰድ ጀመሩ፡፡
የተመረዘው ውኃ የሚመጣው ከአንደኛው አቅጣጫ መሆኑ ሲታወቅ እንስሳቱ ሁሉ አንደኛውን ወንዝ ለመገደብ ተስማሙ፡፡ ይህንን ሃሳብ የተቃወመው ቀበሮ ብቻ ነው፡፡ ቀበሮ ‹‹ይህንን ማድረግ የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር ይጎዳዋል፡፡ የአካባቢው ሥነ ምሕዳር ከሚጎዳ ደግሞ እኛ ብንሠዋ ይሻላል›› ሲል ሃሳብ ሰጥቷል፡፡
አሁንም ቀበሮው በጦርነቱ የራሱ ጫካ መወረሩን ረስቶ የሞቱትን እንስሳት ሥጋ እየሰበሰበ ለጎረቤት ጫካዎች መሸጥ ጀምሯል ይባላል፡፡ ዛሬ ጠዋት ሥጋ ተሸክሞ ከጫካ ሲወጣ በወራሪዎቹ ወታደሮች ተይዞ ነበር፡፡ ‹የአህሉን ቦታ የሚያሳየው ካርታ የት ነው ያለው?›› ተብሎ ሲጠየቅ ‹‹የምን የእህል ካርታ ነው? የተከማቸ እህል መኖሩን ባውቅ እኔ ወደ ሥጋ ንግድ ውስጥ ለምን እገባ ነበር?›› ሲል ነበር መልሶ የጠየቃቸው፡፡ ወታሮቹ ከሄዱ በኋላ ቀበሮ ራሱን ረገመ፡፡ ‹‹ እንዴት ይህንን ነገር እስከ ዛሬ አልሰማሁም? ›› ሲል ተቆጨ፡፡
የሞተው ሞቶ፣ የተሰደደው ተሰድዶ፣ የተረፉትም እየቆሰሉ በየጎሬው ተኝተው ወራሪዎቹ ጫካውን ለቅቀው ወጡ፡፡ አሁን ከባድ የሆነው እነዚያ ለጫካው ሲሉ የቆሰሉና የታመሙ ምን ይብሉ? ምን በልተው ከሕመማቸው ይዳኑ? ምን በልተው ቁስላቸውን ይጠግኑ? የተሰደዱትስ በሄዱበት ይበላሉ፡፡ የሞቱትም ዐርፈዋል፡፡ ካሉት በታች፣ ከሞቱት በላይ ሆነው የተረፉትስ?
አንበሳው ትቶት በሄደው ጫካ የሆነውን ሰምቶ እያገሣና እየደነፋ መጣ፡፡ የነበረው እንዳልነበረ ሆኖም ጠበቀው፡፡ ብዙዎቹ ሞተዋል፤ ሌሎቹ ተሰድደዋል፤ የቀሩትም ቆስለው ተኝተዋል፡፡ በየቤቱ ለተኙትና ለሚያቃስቱት የሚላስና የሚቀመስ ግን አልነበረም፡፡ አንበሳው ወደ ዝንጀሮ ሄዶ የሰጠውን ወረቀት ጠየቀው፡፡ ዝንጀሮው ግን ወረቀቶቹን በኪሎ ከመሸጥ ባለፈ ምንም እንዳላደረጋቸው ተናገረ፡፡ አንበሳው በድንጋጤ ነበር ዐመዱ ቡን ያለው፡፡ ‹‹ለመሆኑ እነዚያ ወረቀቶች ምን ምን እንደያዙ ታውቃለህ?›› አለው፡፡ ዝንጀሮው ግን ‹‹ ጌታዬ ወረቀት መሆናቸውን ካልሆነ በቀር የማውቀው ነገር የለም፡፡ እኔኮ ዝንጀሮ ስለሆንኩና ዛፍ ጫፍ ላይ መውጣት ስለቻልኩ ብቻ ነበር የተሾምኩት፡፡›› ሲል በኀዘን ተናግሯል፡፡
ቢታሰስ ቢታመስ ያ ወረቀት አልተገኘም፡፡ አንበሳው የሚያደርገው ጨንቆት ጎምለል ጎምለል ሲል ድንገት እግሩ ሥር አንዳች ንቅናቄ ተሰማው፡፡ አፈሩ ርግፍግፍ ይላል፡፡ አንዳች አውሬ ከምድር ሥር እየወጣ ነው ብሎ ፈራና ፈቀቅ አለ፡፡ ዓይኑንም ተከለ፡፡ ያ አፈር መሳይ ነገር ረግፎ ረግፎ ወደ ሌላ ቅርጽ ተቀየረ፡፡ ያቺ ዘገምተኛ ዔሊ ነበረች፡፡ አንበሳ ተናደደ፡፡ ‹‹ አንቺ ዘገምተኛ ፍጡር፤ ይህ ሁሉ እንስሳ ሲያልቅ አንቺ እንዴት ተረፍሽ›› አላት፡፡
‹‹ጌታው አይሳሳቱ ፈጣሪ የማይጠቅም ፍጡር አልፈጠረም፡፡ እያንዳንዳችን በሌላ የማይሸፈን አንዳች ቀዳዳ እንድንሞላ የተፈጠርን ነን፡፡ እያንዳንዳችን በሌላ የማይቻል አንዳች ልዩ ችሎታ አለን፡፡ ታላቅነትና ታናሽነት ሥጋን እንጂ ነፍስን አይለካም፡፡ የሥጋ እንጂ የነፍስ ታናሽ የለውም፡፡ ጌታዬ አንዳንድ ጊዜ ታላቅነትና ታናሽነት የአጋጣሚና የዕድል ጉዳይ እንጂ የችሎታ ላይሆን ይችላል፡፡ በዚህ ዓለም ዝሆኑም ትንኙም ያስፈልጋሉ፡፡ በአንድ መሥሪያ ቤት ጥበቃውም፣ መዝገብ ቤቱም፣ የጽዳት ባለሞያውም፣ አትክልተኛውም፣ ተላላኪውም የሥራ አስኪያጁንና የዳይሬክተሩን ያህል ያስፈልጋሉ፡፡ ተራ ሰዎችም የመሪዎችን ያህል ያስፈልጋሉ፡፡ እንዲያውም ዓለምን የሚያድኗትም የሚያጠፏትም ታላላቅ የተባሉ ነገሮች ሳይሆኑ ታናናሽ የተባሉ ነገሮች ናቸው፡፡
‹‹ያ የሚፈልጉት ካርታ የሚገኘው እኔ ዘንድ ነው፡፡ ወራሪዎቹ ሁሉንም ፈትሸዋል፡፡ እኔን ግን አልፈተሹም፡፡ ምክንያቱም አንድም ስለናቁኝ አንድም ራሴን ከመሬት ጋር ቀብሬ ተመሳስዬ ስለነበር፡፡ እኔ ድንጋይ ነበር የምመስላቸው፡፡ ነገር ግን ድንጋይ አልነበርኩም፡፡ የሚፈልጉት ነገር የሚንቁኝ እኔ ዘንድ መኖሩን መጠርጠር ግን አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ካርታውን እርስዎ እስኪመጡ ደበቅኩት፡፡›› አንገቷን ቀስ ብላ አስግጋ ካርታውን አቀበለችው፡፡
‹ትገርሚያለሽ፤ ለመሆኑ አንቺን ምን ብዬ ነበር የሾምኩሽ?›› ሲል በአግራሞት ጠየቃት፡፡
‹‹አይ ጌታዬ እንደ እኔ ዓይነቶቹኮ ሥራውን እንጂ ሹመትና ደሞዙን አናገኘውም›› አለችው፡፡
‹‹አሁን ግን መሾም ያለብሽ አንቺ ነሽ›› አላት፡፡
‹‹የለም ጌታው እንደዚያ አይበሉ፡፡ አሁን ብዙዎች ይመጡና ያዥው ብዬ የሰጠኋት እኔ ነኝ፤ እርሷም እንዳትታይ የደበቅኳት እኔ ነኝ ብለው ዋጋውን አስከፍለውኝ ዋጋውን እንደሚወስዱ ዐውቃለሁ፡፡›› አለችው፡፡ 
© ይህ ጽሑፍ በአዲስ ጉዳይ መጽሔት ላይ የተስተናገደ ነው

Read More

Post your comment

Comments

Be the first to comment

Related Articles

RSS